ራዕያችን እና እምነታችን

በዓለም ዙሪያ ሌት ተቀን፣ የዴሪክ ፕሪንስ ሚኒስትሪስ መጽሐፍ ቅዱስን በማስተማር እንዲሁም፣ የመጽሐፍ ቅዱስን እውነት ለተጠማው ዓለም ሕይወት-ቀያሪ የሆነውን የእግዚአብሔርን ቃል በማካፈል ላይ ይገኛል።

እኛ ማን ነን

የዴሪክ ፕሪንስ ሚኒስትሪሰ ሰዎች ኢየሱስን ሲያገኙ ሕይወታቸው እንደሚለወጥ ያምናል። ደቀመዝሙር በማድረግና በእግዚአብሔር ቃል በሚሰጥ ጤናማ ትምህርት፣አማኞች በዚያ ከጌታ ጋር በመገናኘት በሚገኘው ሙላት ውስጥ እንዲኖሩ አእምሯቸውን እንመግባለን፣ ልባቸውን እናጸናለን እንዲሁም እጃቸውን እንደግፋለን።

ዓለም አቀፋዊ የመጽሐፍ ቅዱስ አስተማሪ የሆኑትን የዴሪክ ፕሪንስ ስምና አሻራ የተሸከመው ይህ አገልግሎት በዓለም ዙሪያ ላሉ አብያተ ክርስቲያናት፣ሚስዮናውያን፣የክርስትና አስተማሪዎችና በሚሊዮን የሚቆጠሩ ምዕመናን ሃብት ሆኖ ያገለግላል። ከ45 በላይ በሆኑ አገራት ውስጥ እና በስድስቱም አህጉራት በተዘረጉ ቢሮዎችና የተለያዩ ተግባራት አማካኝነት፣ የዴሬክ ፕሪንስ ሚኒስትሪስ ላይ መቼም ጸሐይ አትጠልቅም እናም ጥረታችን ደቀ መዛሙርትን ለክርስቶስ ለማፍራት ደቀመዛሙርትን ማስታጠቅ ነው።

ተልእኳችን

የምናደርገው

በየቀኑ መጽሐፍ ቅዱስን እናስተምራለን፤ ምእመናንም በእምነት፣ በጥበብና በእውነት ሙላት ኢየሱስን እንዲከተሉ እናስታጥቃለን።

በዴሪክ ፕሪንስ ሕያው የሆኑ ትምህርቶች አማካኝነት በክርስትና ጉዟቸው በእያንዳንዱ ደረጃና ምዕራፍ ላይ ያሉ አማኞችን ደቀመዝሙር እናደርጋለን። ክርስቶስን ማዕከል ያደረጉና ክልላዊ ቢሮዎቻችን በክርስቲያናዊ እድገት ግንባር ቀደም ሆነው በመሥራት፣ እውነተኛ ለውጥ የሚያመጡ የተለያዩ አገልግሎቶችንና ሃብቶችን በማቅረብ መንፈሳዊ ረሃብን ይዋጋሉ። ይህም የሚከተሉትን ያካትታል፦

የሥልጠና መሪዎች፡-

ከአካባቢው የቤተ ክርስቲያን መሪዎችና መጋቢዎች ጋር በመተባበር፣ መሠረታዊ የሆኑ አገልግሎቶችን ለማጠናከር የሚያስፈልጉ ግብዓቶችንና የትምህርት መሣሪያዎችን እናቀርባለን።

የትምህርት ግብዓቶች፡

በህትመት፣ በቪዲዮ፣ በድምጽ እና በኢንተርኔት የሚገኙ የትምህርት መርጃዎችን አሳትመን በየትኛውም ቦታ ላሉ አማኞች እናደርሳለን። አብዛኛውን የምናዘጋጀውን ቁሳቁስ በነጻ እናከፋፍላለን።

ትርጉም፡

ሕዝብ በሚረዳው ቋንቋ ጤናማ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመሠረተ ትምህርት ማግኘቱን ማየት የእኛ ፍላጎት ነው።

የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ትምህርቶች፡

ለአማኞች ትምህርትና ሥልጠና የሚሆኑ የተለያዩ የተልዕኮ እና የግል ጥናት የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርቶችን እናቀርባለን።

ድጋፍ፡

የእግዚአብሔርን ቃል ኃይልና ሥልጣን እናስፋፋለን፤ ምእመናንም በቤት፣በቤተክርስቲያን፣ በትምህርት ቤትና በቀጥታ የኢንተርኔት መስመር ያላቸውን የመጽሐፍ ቅዱስ እውቀትና ግንዛቤ እንዲያሳድጉ እናበረታታለን።

ፈጠራ፡

የዴሪክ ፕሪንስ ሚኒስትሪስ ባልተለመዱ ፕሮጀክቶችና ተነሳሽነቶች አማካኝነት ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ብዙ ሰዎችን እየደረሰ ነው። የዲጂታል ስብከታችን በማህበራዊ ሚዲያ፣ ቪዲዮዎች፣ ጽሁፎች፣ መተግበሪያዎችና በሌሎችም አማካኝነት በኢንተርኔት የቀጥታ መስመር ላይ ለመገናኘት ቴክኖሎጂን እየተጠቀመ ነው።

ታሪክ

ሁሉም የተጀመረው እ.ኤ.አ በ1971 ዴሪክ ፕሪንስ በፎርት ሎደርዴል፣ፍሎሪዳ በሚገኘው ቤቱ በነበረው ጋራዥ ውስጥ ቢሮ ሲከፍት ነበር። መጀመሪያ ላይ የዴሪክ ፕሪንስ ህትመቶች በመባል የሚታወቀው፣ እ.ኤ.አ በ1944 ጌታ በሚከተለው መንገድ በተናገረው ጊዜ የተጀመረው የዴሪክ የበለጸገ የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት አገልግሎት ውጤት ነበር።

"በእውነትና በእምነት እንዲሁም በክርስቶስ ኢየሱስ ባለ ፍቅር፣ለብዙዎች የመጽሐፍ ቅዱስ አስተማሪ እንድትሆን ተጠርተሃል።"

እነዚህ ቃላት የዴሪክን በመንፈሳዊ ነገር የተራቡትን የመመገብ ጥረት አቀጣጠሉት፣ “ሰልፍ-ስተዲ ባይብል ኮርስ” (እ.ኤ.አ 1969)፣ “ሊበሬቲንግ ትሩዝ” (እ.ኤ.አ 1966)፣ “ሪፔንት ኤንድ ቢሊቭ” (እ.ኤ.አ 1966) እና ሌሎችንም ጨምሮ የተለያዩ መጻሕፍትን እንዲጽፍና ራሱ እንዲያሳትም አነሳሱት። የእነዚህ መጻሕፍት ስኬትና የእግዚአብሔር ታማኝነት ማረጋገጫ እንደመሆኑ መጠን የዴሪክ ፕሪንስ ህትመቶች ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ በመጣው ፍላጎት አደጉ።

እ.ኤ.አ በ1972 ብቻውን ያዘጋጅ የነበረው ሥራ ከዴሪክ አቅም በላይ ሆኖ እያደገ ስለመጣ፣ ዴቪድ ሴልቢ (አማቹ) እንዲረዳው ተጋበዘ። አብረውም እያደገ ለመጣው አገልግሎት የሬዲዮ ስርጭትን በመጀመርና አዳዲስ መጻሕፍትን በማሳተም አቅጣጫ አስቀመጡ።

እ.ኤ.እ በ1980ዎቹ በኒውዚላንድ፣ በደቡብ አፍሪካ፣ በአውስትራሊያ፣ በካናዳ፣ በእንግሊዝ እና በኔዘርላንድስ የውጭ ቢሮዎች ተከፍተው ሕዝቦችን በደቀ መዝሙርነት የማስተማር ሕልሙ እውን ሆነ። በአሥር ዓመቱ መጨረሻ ዴሪክ ሦስት ጊዜ ዓለምን በመዞር የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርትን ሰጥቷል፣ የሬዲዮ ፕሮግራማቸውም በስድስት አህጉራት እና በአሥር ቋንቋዎች በስፋት ተሰራጭቷል።

እ.ኤ.አ በ1990 ዓ.ም. የዴሪክ ፕሪንስ ህትመት በይፋ ወደ ዴሪክ ፕሪንስ ሚኒስትሪስ ተቀየረ። የነጻ የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ቁሳቁሶች ስርጭት ተጠናክሮ በአጠቃላይ 140 አገሮችን የደረሰ ሲሆን የዴሪክ መጻሕፍትም ከ50 በሚበልጡ ቋንቋዎች ተተርጉመው ይገኛሉ።

ዴሪክ ፕሪንስ ሚኒስትሪስ ዛሬ በዓለም ዙሪያ ከ45 በላይ በሆኑ አገራት ቢሮዎች ያሉት ሲሆን በየሃገሩ፣ በየባህሉና በየቋንቋው የመጽሐፍ ቅዱስን ትምህርት ለማስተማር በሙሉ ልቡ ቁርጠኛ ሆኖ ቀጥሏል። የአገልግሎቱ እድገትና ስኬት ጌታ እ.ኤ.አ በ1941 ለዴሪክ የተናገረውን ትንቢታዊ ቃል ያረጋግጣል፤ በዚያን ጊዜ ጌታ እንዲህ ብሎታል፦

እንደ ትንሽ ጅረት ይሆናል። ጅረቱም ወንዝ ይሆናል። ወንዙም ትልቅ ወንዝ ይሆናል። ትልቁ ወንዝም ባሕር ይሆናል። ባሕሩም ታላቅ ውቅያኖስ ይሆናል፥ ይህም በአንተ በኩል ይሆናል፤ ነገር ግን እንዴት እንደሚሆን ማወቅ የለብህም፥ ማወቅም አትችልም፥ ልታውቅም አይገባህም።

እግዚአብሔር ለዚህ ቃል ያለው ታማኝነት የዴሪክ ፕሪንስ ሚኒስትሪስን ዛሬ ላለበት ደረጃ ያደረሰው ሲሆን ወደፊትም አገልግሎቱን ወደ “ታላቅ ውቅያኖስ” ማሳደጉን የሚቀጥል ይሆናል።

በደሬክ ፕሪንስ የተዘጋጁ በርካታ የጽሑፍ፣ የድምጽ እና የምስል መረጃዎችን በመጠቀም፣ አገልግሎቱ አዳዲስ መጻሕፍትን ማሳተም ቀጥሏል። እስከዛሬ ድረስ ከ100 በላይ መጻሕፍት ታትመው ከ100 በላይ በሆኑ ቋንቋዎች ተተርጉመዋል።

የምናምነው

የእምነት መግለጫ።

  • እግዚአብሔር አንድ እውነተኛ ሕያው አምላክ ሲሆን፤ ከዘላለም እስከ ዘላለም በሦስት አካላት አብ፣ ወልድና መንፈስ ቅዱስ ይኖራል፤ እርሱም መንፈስ፣ ወሰን የሌለው፣ ዘላለማዊ፣ በፍቅሩ፣ በምሕረቱ፣ በኃይሉ፣ በጥበቡና በጽድቁ የማይለወጥ ነው።1
  • ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ ነው፤ ከድንግል ተወልዶ ሥጋ ለበሰ፤በመለኮቱም በሰውነቱም ፍጹም ነው፤ ስለ ሰው ኃጢአት ፍጹምና ሁሉ በሁሉ የሆነ የቤዛነት መሥዋዕት ሆኖ ሕይወቱን በፈቃዱ ሰጠ፤ በእርሱ ቤዛነት ሰው ከኃጢአት ቅጣት፣ ከጥፋተኝነትና ከሚያስከትለው ውጤቱ ነፃ መሆን ይችላል፤ ከሙታን በተነሣበት አካላዊና በከበረ ሥጋው አሁን በሰማይ ተቀምጦ ስለ አማኞች ይማልዳል፤ እንዲሁም መንግሥቱን ሊመሰርት በከበረ ሥጋው ዳግመኛ ይመጣል።2
  • መንፈስ ቅዱስ ከእግዚአብሔር አብ እና ከእግዚአብሔር ወልድ ጋር በመለኮት ባሕርያት ሁሉ እኩል ነው፤ ክርስቶስን አዳኝ አድርገው በሚቀበሉት ውስጥ የዳግም መወለድን ተአምር ይሠራል፤ አሁንም በአማኞች ውስጥ ይኖራል፤ እስከ ቤዛ ቀን ድረስ ያትማቸዋል፤ ለአገልግሎት ያስታጥቃቸዋል፤ የክርስቶስን አካል ለማነጽ የጸጋ ስጦታዎችን (ካሪዝማቲክ ስጦታዎችን) ይሰጣል።3
  • እውነት የማይለወጥና ፍጹም ነው። የሚያድነው እውነት ከእግዚአብሔር ዘንድ ለሰው ልጅ በጽሑፍ በቀረበው፤ በቃል መንፈስ አነሣሽነት እና በመጀመሪያዎቹ ቅጂዎች ያለምንም ስህተት በተቀመጠው በብሉይ እና በአዲስ ኪዳን መጻሕፍት ውስጥ ተገልጿል። መጽሐፍ ቅዱስ በእምነትና በተግባር ጉዳዮች ሁሉ የበላይ እና የመጨረሻው ባለሥልጣን ነው።4
  • ቤተክርስቲያን በምድር ላይ የተዋሃደ የክርስቶስ አካል ስትሆን፣ለኅብረት፣ለመታነጽ እና በክርስቲያናዊ ሕይወትና ምስክርነት ወንጌልን ለአሕዛብ ሁሉ ለማድረስ ትኖራለች።5
  • ሰው በእግዚአብሔር መልክ ተፈጥሮአል፥ ነገር ግን በአዳም ኃጢአት ከእግዚአብሔር ተለይቶ ለዘላለም ቅጣት ተፈርዶበታል። የሰው ችግር ብቸኛው መፍትሔ በኢየሱስ ክርስቶስ ማንነትና ሥራ በግል እምነት መዳን ነው።6
  • ውሱን ከተፈጥሮ በላይ የሆኑ ግላዊ ፍጡራን አሉ፤ እነዚህም ያልወደቁ መላእክትን፣ የወደቁ መላእክትንና አጋንንትን ያካትታሉ። የወደቁት መላእክት መሪ ሰይጣን የእግዚአብሔርና የሰው ልጅ ግልጽና የተገለጸ ጠላት ሲሆን በእሳት ባሕር ለፍርድ ተወስኗል።7
  • የዳኑትም የጠፉትም በሥጋ ይነሣሉ፤ የዳኑት ለዘላለም ሕይወት፥ የጠፉት ደግሞ ለዘላለም ፍርድ።8
  1. ኢሳይያስ 45:22፤ መዝሙር 90:2፤ ዮሐንስ 4:24፤ 2ኛ ቆሮንቶስ 13:14
  2. ማቴዎስ 1:18–25፤ ዮሐንስ 1:14፤ ቆላስይስ 1:13–18፤ 1ኛ ጴጥሮስ 2:24፤ ሉቃስ 24፤ ዕብራውያን 4:14፤ ማቴዎስ 25:31–46
  3. ኤፌሶን 4:30፤ 1ኛ ቆሮንቶስ 6:19፤ 12:4, 7, 12–13፤ የሐዋርያት ሥራ 1:5፤ ቲቶ 3:5
  4. ማቴዎስ 5:18፤ 2ኛ ጢሞቴዎስ 3:15–17፤ 2ኛ ጴጥሮስ 1:20–21
  5. ማቴዎስ 28:19-20፤ የሐዋርያት ሥራ 1:6-8፣ 2:41-42፤ 1ኛ ቆሮንቶስ 12:13
  6. ዮሐንስ 3:15–18፤ ኤፌሶን 1:7፤ ሮሜ 10:9–10
  7. ዕብራውያን 1:4-14፤ ይሁዳ 6፤ ማቴዎስ 25:41፤ ራእይ 20:10
  8. 1ኛ ቆሮንቶስ 15፤ ዳንኤል 12፥1-2፤ ዮሐንስ 5፥28-29፤ 2ኛ ተሰሎንቄ 1፥7፤ ማቴዎስ 5፥1-10
መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ቃል ነው። በየትኛውም ስፍራ ላለ ሰው ሁሉ የቀረበ የእግዚአብሔር ታላቅ ስጦታ ነው።

ዴሪክ ልዑል